Tuesday, November 24, 2020

ቅዱስ ቴዎድሮስ ካቴዲራል ቤተ ክርስቲያን

 ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ በሸዋ ሮቢት ከተማ በቅዱስ ቴዎድሮስ ካቴዲራል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ለምእመናን ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሰጡ።

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪና የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንትና የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሸዋ ሮቢት ከተማ ቅዱስ ቴዎድርስ ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ለምእመናን ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሰጥተዋል።

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ በቦታው ሲደርሱ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ በሰንበት ትምህርት ዘማርያንና በርካታ ምእመናን በዝማሬ ፣ በእልልታና በጭብጨባ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል።

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሁሉን ማድረግ የሚቻለው አምላካችን በፍቅሩ ስቦ በረድኤት ጠብቆ የበረከት ፣ የፍቅርና የሰላም ተምሳሌት ከሆናችሁት የሸዋ ሮቢት ምእመናን ጋር በመገናኘታችን ደስ ብሎናል እናንተም እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

እናንተ ከክፉ ነገር የራቀ የመልካም ነገገር የሁሉ መጠለያና ማረፊያ የተባረከ የመንገድ ዳር ሾላ ናችሁ ፤ በካህናትና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት በኔ ኑሩ እኔም በእናንተ እኖራለሁ የሚለውን አምላካዊ ቃል በመፈጸም ጣፋጭ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ የህይወት ልምላሜ የታዬባችሁ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር የለዩ የቅዱሳን አባቶቻችን ልጆች ናችሁ ብለዋል።

በተመሳሳይ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ባስተላለፉት መልእክት ዘመናትን አሳልፎ የሚኖር ኃጢአትና በደላችንን ሳይቆጥር በእድሜያችን ላይ ይኽን ጊዜ ጨምሮ ከጨለማ ወደ ብርሃን እንድንሸጋገር ያደረገ በቅድስናው ስፍራ በሰማያዊት ምድር ተሰብስበን ስሙን እንድናመሰግን የፈቀደልን የቅዱሳን አምላክ ክብርና ምስጋና ይግባው ብለዋል።

"ልጆቼ ሆይ ታገለግሉት ዘንድ ከፊቱም ቀርባችሁ ለእርሱ በመታመን መልካሙንና በጎ ነገርን ትፈጽሙ ዘንድ እርሱ እግዚከብሔር መርጧችኋልና ቸል አትበሉ" በሚል ርዕስ የቀድሞዎቹ አባቶቻችን በፍቅርና በመተባበር የነበራቸውን አምልኮተ እግዚአብሔርን አሁን ያሉት አንዳንዶች ይኽንን ትተው የበጎ ሥራ መንገዶች ተቆፋፍረውና የአመጽ መንገዶች ተከፍተው የሰው ልጅ ከአምላኩ ይልቅ ስልጣን፣ ገንዘብንና ሰውን መደገፍ ቢጀምርም ሁሉም የሚያልፉ በመሆናቸው ይወድቃሉ እግዚአብሔርን የሚደገፉ ግን አይወድቁም አያቶቻችሁን ዋኖቹን አስቡ ብለዋል።

ምእመናን በችግር መካከል የበቀልን ነን ችግር ዙሪያችንን ከቦናል መልካምም ነገር አንሰማም ስናለቅስ እንባችንን የሚያብስልን ሳይሆን በልቅሷችን ላይ ሌላ ሀዘን ይጨምሩብናል ነገር ግንጌታችንና አምላካችን አይዛችሁ ልባችሁ አይታወክ በእኔ እመኑ እኔም ከእናንተ ጋር እሆናለሁ አባት እንደሌለው ልጅ አልተዋችሁም ብሏልና እግዚአብሔር ሕዝቡን ነጻ ለማውጣት ሠራዊት አይመለምልም ሲሉ ምእናኑን መክረዋል።

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስበከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ክቡር መጋቤ ሐዲስ ነቅዐጥበብ አባቡ "በረከትን ትወርሱ ዘንድ በዚህ ተጠርታችኋል"
በሚል ርዕስ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን በዚሁ ቤተ ክርስቲያን በስርአተ ተክሊል ጋብቻቸውን የፈጸሙት እደለኞቹ ሙሽሮች በድገት በተገኙት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋብቻቸው ተባርኮላቸዋል።



ፈጣን መረጃ ለማግኘት የቴሌግራም ቻናላችን ይቀላቀሉ
https://t.me/EOTCNSD
website: https://eotcnorthshoadiocese.blogspot.com/








Sunday, November 22, 2020

በ፰ ነጥብ ፪ ሚሊዮን ብር የሕንጻ እድሳት

በከተማዋ ነዋሪዎችና በአካባቢው ተወላጆች በ፰ ነጥብ ፪ ሚሊዮን ብር የሕንጻ እድሳትና የማስፋፊያ ስራ የተደረገለት የመሐል ሜዳ ደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴዲራል በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ቅዳሴ ቤቱ በዛሬው ዕለት በታላቅ ድምቀት ተከበረ።

የቅዱስ ሚካኤል ጽላት ከ፲ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በደዋት ልደታ በድርብነት የነበረ ሲሆን በ1947 ዓ.ም እንደተመሰረተች የሚነግራላት ባለዘመናዊ ፕላኗ መሀል ሜዳ ከተማ ምእመናን ጥያቄ አሁን ባለበት የከተማ እምብርት የተተከለው ካቴዲራሉ በተለያዩ ጊዜያት ግንባታው ሲካሄድ ቆይቶ ባጋጠመው የግንባታ የጥራት ችግር በ፰ ነጥብ ፪ ሚሊዮን ብር የሕንጻ እድሳትና ማስፋፋት ተደርጎለት በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ በርካታ ሊቃውተ ቤተ ክርስቲያን እና በ፲ሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በተገኙበት በዛሬው ቤተ መቅደሱ ከዓመታዊ ክብረ በዓሉ ጋር ተቀናጅቶ በታላቅ ድምቀት ተክብሯል።

በክብረ በዓሉ ላይ ለተሰበሰቡት ምእመናን ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ፓትያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የበላይ ጠባቂና የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ አስተላልፈዋል።

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የደስታ ቃል በጻድቃንና በደጋጎች ቤት ነው ፤ በጎና መልካም የሆነ ለሀገር የሚበጅ ስራ የሚሰሩ ሰዎች በረከተ እእግዚአብሔር በቤታቸው ነው ፣ ቆራጦችና ደጋጎቹ የእግዚአብሔር ሰዎች ከእግዚአብሔርም ከሰውም በረከት ያገኛሉ እናንተ ደግሞ በአባ ገብረ ናዝራዊ ዘመን 1ሺህ 5መቶ የሚሆኑ መነኮሳት በአጋንቺ ኪዳነ ምህረት የሚጸልዩበት የቅዱሳን ልጆችና የበረከት ፍሬዎች ናችሁ ብለዋል።

አምላካችን እግዚአብሔር ሰው በጠፋበት ጊዜ እንደ ሙሴ አይነት መልካሞችን በማስነሳት እስራኤላውያንን ነጻ እንዳወጣቸው ሁሉ ይኽንን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በመገንባት ለፍጻሜ ያበቃችሁ የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴዎች ፣ የከተማዋ ነዋሪዎችና በተለያዩ ቦታዎች ለሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች የዘመናችን ሙሴዎች ናችሁ ሲሉ ብፁዕነታቸው ምስጋና አቅርበዋል።

በተመሳሳይ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ብዙዎች እናንተን ለማየት ሽተው አላዩም እናንተንና በሁሉ ነገር የደከማችሁበትን የድካማችሁ ፍሬ የሆነውን ይኽን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን የሰሙ ጆሮዎቻችን ፣ ያዩ አይኖቻችንና የረገጡ እግሮቻችን የተባረኩ ናቸው በዓሉን ከናንተ ጋር በማክበራችን በእጅጉ ተደስተናል እናንተም እንኳን ለዚህ አበቃችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

መንዝና አካባቢው የነገስታት መሰወሪያና በዮዲት ጉዲት ዘመን ያልታቀጠሉ አብያተ ክርስቲያናት መገኛ ነው ያሉት ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ

በአባቶችሽ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ እንዳለ ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት እናንተም በእምነት ፣ በእውቀትና በእውነት የተወለዳችሁ  የቅዱሳን ልጆች ናችሁ ብለዋል። 

"ያገለግለኝ ዘንድ ሕዝቤን ልቀቅ" በሚል ርዕስ የዕለቱን ወንጌል ያስተማሩት የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ክቡር መጋቤ ሐዲስ ነቅዐጥበብ አባቡ በችግር ምክንያት ወደ ግብጽ የተሰደዱት እስራኤላውያን ለ430 ዓመታት በስቃይና በመከራ ቆይተው አምላካችን እግዚአብሔር በሙሴ አማካኝነት ሌሊቱን በብርሃነ እሳት ቀኑን በደመና በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት ከፈርኦን ግዛት ነጻ መውጣታቸውን ገልጸው ዛሬም እንደፈርኦን በሀገራችን ደም የጠማቸውን ደም አፍሳሾች አምላከ ቅዱሳን ያስታግስልን ሲሉ በስፋትና በምልአት አስተምረዋል።

የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ ሊቀ መንበር የሆኑት አቶ ካሳዬ ወልደ ማርያም ባቀረቡት ሪፖርት የዛሬው ቀን ዓመታትን ያስቆጠረው ጭንቀታችን እልባት ያገኘበትና በመተባበር ተአምር መስራት እንደምንችል ከብዙ ድካም በኋላ ያስመሰከርንበት የድል ቀን ሲሆን የዚህ ካቴዲራል የማስፋፋትና የእድሳት ስራ ሊጠናቀቅ የቻለው በጸሎትና በእቅድ መመራቱ መሆኑን ጠቁመውና እስካሁን ግንባታው ፰ ነጥብ ፪ ሚሊዮን ብር መፍጀቱን ገልጸው ለግንባታው የገንዘብ ፣ የአይነት ፣ የገንዘብና የጉልበት ድጋፍ በውጭና በሀገር ውስጥ ለሚገኙ የአካባቢው ተወላጆችና ለመሀል ሜዳ ከተማ ነዋሪዎች ምስጋና አቅርበዋል።

ለግንባታው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላ የሽልማትና የሰርተፍኬት ስጦታ ተበርክቶላቸዋል።

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በታሪክ የታወቁ በዓለም የተደነቁ አድባራትና ገዳማት መገኛ ሲሆን ከነዚህም መካከል የመሀል ሜዳ ደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴዲራል አንዱ ነው።